(ክፍል ፭ ጠያቂ ትምህርት)
✍ ዮሴፍ ኢትዮጵያ | አልፋና ዖሜጋ ዘተዋሕዶ
በቀድሞ ዘመን፣ ኪሚሮስ የተባለ አንድ ሰው ነበር። መጀመሪያውኑ እንደማንኛውም ሰው የነበረ ቢሆንም፣ በአጋጣሚዎች በውስጡ የገባው ርኩስ መንፈስና የኃጢአት ጨለማ ሰብእናውን ቀስ በቀስ ገፈፈው። ርኅራኄ ከልቡ ውስጥ ነጥፎ ደረቀ። በመጨረሻም አእምሮው ተናወጠ፤ የሰው ሥጋ መብላትና ደም መጠጣት ጀመረ።
ከገዛ ቤተሰቡ ጀምሮ፣ ወዳጅ ዘመዶቹን፣ አገልጋዮቹን፣ በመጨረሻም በመንገድ የሚያልፈውን መንገደኛ ሁሉ እያደነ መብላት ጀመረ። ኪሚሮስ "በላኤ ሰብዕ" (ሰውን የሚበላ) የሚል አስፈሪ ስም ተሰጠው። በአጠቃላይ ሰባ ስምንት (78) ሰዎችን በላ። ስሙ ሲጠራ ነፍሰ ጡሮች ይጨነግፋሉ፣ ጀግኖች ይንቀጠቀጣሉ። እርሱ በሚያልፍበት ሸለቆ ሁሉ የሞት ሽታ ይገነፍል ነበር። ሰው መሆኑ አብቅቶ፣ የገሃነም ደጃፍ ጠባቂ አውሬ መሰለ።
አንድ ቀን፣ በላኤ ሰብዕ ጦሩን አንግቦ፣ የውኃ ኮዳውን አንጠልጥሎ፣ ሌላ ሰለባ እየፈለገ በጠራራ ፀሐይ ሲጓዝ፣ አንድ በለምጽ የተመታ፣ በረኃብና በጥም የደከመ ምስኪን ለማኝ በመንገዱ ላይ አገኘ። ለማኙ ሰውነቱ ቆስሎ ሥጋው ስለረገፈ፣ በላኤ ሰብዕ ሊበላው አላስመኘውም። በንቀት አልፎት ሊሄድ ሲል፣ ለማኙ በተሰነጠቀ ድምፁ፣ "ጌታዬ ሆይ፣ ከጥም የተነሣ ነፍሴ ልትወጣ ነውና እባክህ በፈጣሪ ስም አንዲት ጠብታ ውኃ አጠጣኝ" ብሎ ለመነው።
ለማኙ ቀጠለ፦ "በጻድቃን ስም... በሰማዕታት ስም..." አሁንም ኪሚሮስ የጭካኔ ሳቅ ሳቀ እንጂ ልቡ አልራራም። ሁሉም የሰማይ ስሞች በዚያ የድንጋይ ልብ ላይ ተንከባለሉ እንጂ አንዳች አልፈጠሩም።
ለማኙ የመጨረሻዋ የሕይወቱ እስትንፋስ ልትወጣ ስትል፣ አንዲት የመጨረሻ ስም ጠራ፦ "እባክህ... ስለ ኪዳነ ምሕረት፣ ስለ አምላክ እናት ብለህ አንዲት ጠብታ ውኃ በጉሮሮዬ አፍስስልኝ!"
ድንገት... የሞት ሸለቆ ጸጥ አለ። ያ ሰባ ስምንት ሰዎችን የበላው አውሬ፣ እግሩ መሬት ላይ ተገተረ። "ኪዳነ ምሕረት" የሚለው ስም እንደ መብረቅ ወርዶ የድንጋይ ልቡን ሰነጠቀው። በዚያች ቅጽበት፣ በውስጡ የነበረው ርኅራኄ አልባ ጨለማ ለአንዲት ሴኮንድ ተገፈፈ። በላኤ ሰብዕ ወደ ለማኙ ጠጋ ብሎ፣ ከኮዳው ውስጥ አንዲት ጠብታ ውኃ በለማኙ የደረቀ ከንፈር ላይ አፈሰሰ። ከዚያም መንገዱን ቀጠለ።
ብዙም ሳይቆይ በላኤ ሰብዕ ሞተ። ነፍሱ ከሥጋው ስትለይ፣ የገሃነም አጋንንት በታላቅ ጩኸትና ፌሽታ መጡ። "ይህማ የእኛ ነው! 78 የፈጣሪን ፍጥረታት የበላ አውሬ ነው!" እያሉ ነፍሱን እየጎተቱ ወደ ፍርድ አደባባይ አቀረቡት።
ሚዛን ቆመ። በግራ በኩል፣ ሰባ ስምንት የተበሉ ሰዎች ደም፣ አጥንትና የጭንቅ ጩኸት ተቀመጠ። ሚዛኑ ወደ ገሃነም ጥልቀት ዘቀጠ። በላኤ ሰብዕ የሚድነበት ምንም ዓይነት ተስፋ አልነበረም። የጽድቅ ሥራ የሚባል አንዳች ነገር አልነበረውምና። አጋንንት ሊወስዱት እጃቸውን ዘረጉ።
ያን ጊዜ፣ ከሰማያት በላይ፣ ግርማዋ የሚያንቀጠቅጥ፣ መዓዛዋ የገነት የሆነ፣ የብርሃን እናት—ድንግል ማርያም (ኪዳነ ምሕረት) ወደ ፍርድ ዙፋኑ ቀረበች። "ይህች ነፍስ የእኔ ናት!" አለች። አጋንንት በግርምት አፈጠጡ፤ "እንዴት? ሰባ ስምንት ሰው የበላ ነፍሰ ገዳይ እንዴት ያንቺ ይሆናል?" ብለው ሞገቱ።
እመቤታችንም ያቺን በላኤ ሰብዕ በስሟ የሰጣትን አንዲት ጠብታ ውኃ በእጇ ይዛ አወጣች። በዚያች ጠብታ ውኃ ውስጥ፣ ስለ ስሟ የተደረገው የፍቅር ክብደት፣ እና ለማኙ የተነፈሰባት የሕይወት ትንፋሽ ነበረችበት። ያቺን አንዲት ጠብታ ውኃ በቀኝ ሚዛን ላይ አስቀመጠቻት።
በዚያች ቅጽበት፣ መላእክት በግርምት የፊታቸውን ላብ ጠረጉ፤ አጋንንት በድንጋጤ ወደ ኋላ አፈገፈጉ። ያቺ አንዲት ጠብታ ውኃ... ሰባ ስምንቱን የሞት ክምር ወደ ላይ አንፈራጠረችው። የሚዛኑን ክብደት አሸነፈችው! የኪዳነ ምሕረት ቃል ኪዳን ከኃጢአት ሁሉ በላይ ከፍ ብሎ ታየ። በላኤ ሰብዕ፣ በአንዲት ጠብታ ውኃ፣ ስለ አምላክ እናት ስም በተደረገችው ትንሽዬ የርኅራኄ ሥራ ከገሃነም እሳት ዳነ!
እነሆ ማጠቃለያ የቤት ሥራ... ለእኔም/ለአንተም/ ለአንችም፦
የሕሊና ማነቂያ (የሕይወት ጥያቄዎች ወደ አንባቢው)፦
ወዳጄ ሆይ... ይህ ትረካ የጥንት ዘመን ተረት አይደለም፤ ዛሬም በአንተና በእኔ ውስጥ የሚሠራ የሕይወት እውነት እንጂ።
▫ የአንተ ከሳሾችህ 78 የሞት ሰለባዎች ምንድን ናቸው? በገዛ አንደበትህ የገደልካቸው (ያማሃቸው) ሰዎች፣ ያፈረስከው ትዳር፣ የሰበርከው ልብ፣ በክፋትህ የበላኸው የሌሎች ተስፋ ሊሆን አይችልም?
▫ እግዚአብሔር ሲመዘንህ፣ በሚዛኑ ግራ በኩል የሚያስቀምጠው የኃጢአትህ ክምር ምን ያህል ይከብድ ይሆን?
🔔 ነገር ግን ታላቁ ጥያቄ ይህ ነው፦ በሚዛንህ ቀኝ በኩል የምትቀመጥ ያቺ "አንዲት ጠብታ ውኃ" አለችህ? በጥፋትህ መካከል፣ ለእግዚአብሔር ወይም ለእመቤታችን ፍቅር ብለህ ያደረግሃት አንዲት የንጹሕ ርኅራኄ ጠብታ አለችህ ወይስ ኮዳህ ሙሉ በሙሉ ደርቋል?
ወዳጄ፡መልስ ያስፈልግሃል!
የኃጢአትህ ብዛት የቱንም ያህል ቢከብድ፣ ከእግዚአብሔር የምሕረት ውቅያኖስና ከእናቱ ቃል ኪዳን ሊበልጥ ፈጽሞ አይችልም። ዛሬውኑ ያቺን አንዲት ጠብታ ውኃ አፍስስ!
0 Comments