ንግሥናን ከቅስና አጣምሮ የያዘውን የአባቶቻችንን ግርማሞገስ ተፈጥሮውን፣ አባወራነት እሴቱን ጥሎ፤ በብሶትና በእንከፍ ምስኪንነት፣ በጃንደርብነትም እንዲጠፋ ለተፈረደበት ትውልዴ!
አውሮፓውያን በጨለማው ዘመን በጭንቅ ተከበው፣ የመስቀል ጦርነት አውድማ ላይ ኾነው “ተስፋ” አድርገው የሚጠብቁት አንድ ታላቅ ንጉሥ ነበር።
እርሱም “ቀሲስ ዮሐንስ” (Prester John) ይባላል። ዓለም በግርማው የተደመመችለት፣ ቅስናን (ቅድስናን) ከንግሥና (ኃይል) ጋር አጣምሮ የያዘ፣ ለጽድቅ የሚጨክን ልብና ለሀገር የሚቆም ወኔ ያለው “አባወራ” መሪ ነበር።
ያኔ ነጮቹ “ትድግና ከእርሱ ዘንድ ትምጣልን” ብለው በናፍቆት የተመለከቷት ኢትዮጵያ፣ ዛሬ ግን የገዛ ልጆቿ፣ ያውም የተማሩቱ “ኋላ ቀር” ብለው የሚጸየፏትና ለማፍረስ የሚሽቀዳደሙባት የባንዳዎች መናኻሪያ ኾናለች።
ያ ትውልድ ንግሥናን ከቅስና አጣምሮ የያዘ፣ ባለግርማና ባለሃይማኖት ነበር። ዛሬ ግን ያ ግርማው ተገፎ፣ በምትኩ “ምስኪንነት” እና “ጃንደርብነቱ” እንደ “ዘመናዊነትና መንፈሳዊነቱ” የሚሸጡለት ዘመን ላይ ደርሰናል።
ትውልዱ የባዕዳን ማርክሳውያኑ በሚረጩት የብሶት ትርክት ተመርዞ፣ ራሱን እንደ ኃያል ባለቤት ማየቱ አንባገነን በዳይነት ተብሎ፣ እንደ ምስኪን ተመጽዋች እንዲቆጥር ተፈርዶበታል።
አባቶቻችን በጸሎትና በጦር ዓለምን ሲያስደምሙ፣ የዛሬው ትውልድ ግን በ”መብትና በእኩልነት” ሰበብ ወንድነቱን አምክኖ፣ ወኔልቡን ሰልቦ፣ አባወራነቱን ጥሎ፣ የባዕዳን አጀንዳ አሳላጭ እንደነእርሱም ዘርአልባ “ጃንደርባ” ኾኖ ታጅሯል።
“LE GRAND NEGUS — PRETE IAN” (ታላቁ ንጉሥ — ቄስ ዮሐንስ)
ከሥሩ ያለው ዝርዝር ጽሑፍ ደግሞ የንጉሡን ማንነት፣ ግርማና ግዛት በሚከተለው መልኩ ይገልጻል፦ማንነቱ፦ “የአቢሲኒያውያን ንጉሠ ነገሥት” (Empereur des Abissins) በማለት ይጀምርና፣ ንጉሡ ከንጉሥ ሰሎሞንና ከንግሥተ ሳባ የተወለደ የዳዊት ዘር እንደሆነ ይገልጻል። ይህ የሚያሳየው አውሮፓውያን የኢትዮጵያን ነገሥታት ከቅዱስ መጽሐፍ ታሪክ ጋር በማያያዝ ምን ያህል ትልቅ ክብር ይሰጡ እንደነበር ነው።
ሥልጣኑ፦ በጽሑፉ ላይ ንጉሡ የሰባ ነገሥታት የበላይ ወይም “የነገሥታት ንጉሥ” (Roi des Rois) እንደሆነ ተጠቅሷል።
ጦረኝነቱ፦ በእጁ የያዘው በትረ-መንግሥት (Scepter) ጫፉ ላይ የመስቀል ቅርጽ ያለው ሲሆን፣ ይህ ደግሞ “ኃይሉ በሃይማኖቱ ላይ የተመሠረተ ጦረኛ ንጉሥ” መሆኑን ያሳያል። የለበሰው ልብስም የጦር ትጥቅ (Armor) እና ንጉሣዊ ካባ ጥምረት ነው።
ግዛቱ፦ ግዛቱ እስከ ቀይ ባሕርና አባይ ወንዝ ድረስ የሚዘልቅ፣ እጅግ ሰፊና ለም መሬት እንደሆነ ይተርካል።
ወንድምዓለም! አባቶችህ ተከበሩት፣ የጦር ሰይፋቸውን ከጸሎት መስቀላቸው ጋር፣ ምድራዊ ሥልጣናቸውን ከመንፈሳዊ ማንነታቸው ጋር አስተሳስረው ስለያዙ ነው።
አንተ ግን ስልብ ጃንደርብነትን መንፈሳዊነት፣ እንከፍ ምስኪንነትን ዘመናዊነት አድርገህ የራስህ ሳያንስ ትውዱን ለባርነትና ሞቱ ትማግዳለህ!
ጃንደርባ ማለት የተሰለበ፣ መውለድና መቀጠል የማይችል፣ ለጌቶቹ ታዛዥ እንዲኾን ወኔ ብልቱ የተበላሸ የተኮላሸ ትውልድ ማለት ነው።
የትውልዱ"የመንፈስም ጃንደርብነት" የሚያበቃው፣ እንዲህ ያለውን የጥንት ማንነቱንና በአውሮፓውያን ዘንድ የነበረውን "የተስፋ ጮራ" የመኾን ታሪኩን ዳግም መመርመር ማወቅና መኖር ሲችል ነው።
ዛሬም በትምህርት፣ በዘመናዊነትና በመንፈሳዊነት ካባ ተሸፍነው የሚመጡት የባዕድ ትርክቶች ዋና ዓላማቸው ትውልዱን “ሥነ-ልቦናዊ ጃንደርባ” ማድረግ ነው።
👉 ካህናዊ ቅድስናውን ነጥቀው “አልጫ” አደረጉት፤
👉 ንጉሣዊ ግርማውን ሰልበው “ታዛዥና አጎንባሽ ጃንድርባም” አደረጉት፤
👉 አባወራነቱን አጥፍተው “ትውልድ አልባ፣ ቤተሰብ አልባ” አደረጉት።
ይህ ትውልድ ምን “ዶክትሬትና ማስትሬት” ቢጫንም፣ ልቡ ግን ከማንነቱ ጋር ተጣልቷል፣ ተለያይቷል። በጠላቶቹ ፊት አንገቱን የሚደፋ፣ ለባዕድ ፍርፋሪ ሀገሩንና እሴቱን የሚቸረችር፣ የጃንደርባነት፦ አጎንባሽ አጎብዳጅነት አባዜ የተጠናወተው ኾኗል።
የካህኑ ዮሐንስ ግርማዊነት ዛሬ ለዚህ ትውልድ እንደ ተረት ሊርቅበት፣ እንደ ምስጢር ሊረቅበት ይችላል። ምክንያቱም የታወረ ዐይን ብርሃንን ማየት አይችልም፤ የተሰለበ ልብም ግርማን ሞግስን፣ ጽድቅ መፈጸም የሚችል ወኔን አይረዳም።
ስለ እርሱ እንዲህ መባሉን ምን ያክል ታውቃላችሁ?
1ኛ ንግሥናን ከቅስና አጣምሮ የያዘ (The Priest-King)
የካህኑ ዮሐንስ ዋነኛ መለያው “ንጉሥም ካህንም” መኾኑ ነው። በምዕራቡ ዓለም ሥልጣን በቤተ-መንግሥትና በቤተ-ክህነት መካከል ተከፋፍሎ (በነገሥታትና በሊቀ-ጳጳሳት መካካል ግጭት በነበረበት ዘመን)፣ እርሱ ግን ምድራዊውን ሥልጣን ከሰማያዊው እምነት ጋር ያስታረቀ፣ ባለ ግርማና ቅዱስ መሪ ተደርጎ ይታመን ነበር።
2. እጅግ ባለጸጋና ብርቱ ኃይል ያለው
ካህኑ ዮሐንስ የሚገዛው ግዛት በወርቅ፣ በዕንቁና በልዩ ልዩ ማዕድናት የበለጸገ እንደኾነ ይታመን ነበር። “በመንግሥቱ ውስጥ ሌባና ውሸታም የለም፣ ድሃም አይገኝም” ተብሎ ይወራለት ነበር። በጦርነትም ቢኾን 72 ገባር ነገሥታት የሚገዙለትና የማይበገር ሠራዊት ያለው ታላቅ ኃይል ተደርጎ ይታወቅ ነበር።
3. የክርስቲያን አጋርና “ታዳጊ”
አውሮፓውያን በእስልምና ኃይሎች ተከብበውና ተዳክመው በነበረበት ወቅት፣ ካህኑ ዮሐንስ ከምስራቅ በኩል መጥቶ እስልምናን ድል በማድረግ ክርስቲያኖችን ነፃ ያወጣቸዋል ተብሎ ተስፋ ይደረግ ነበር። ይህ ስሙና ዝናው ለአውሮፓውያን የሞራል ጋሻ ሆኖ ለዘመናት አገልግሏል።
4. ከኢትዮጵያ (አቢሲኒያ) ጋር ያለው ቁርኝት
መጀመሪያ ላይ በእስያ (ሕንድ) ይገኛል ተብሎ ቢታሰብም፣ በ14ኛው ክፍለ ዘመን አካባቢ አውሮፓውያን ስለ ኢትዮጵያ ጥንታዊ ክርስቲያን መንግሥት ሲረዱ፣ ካህኑ ዮሐንስ ያለው ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሆነ በጽኑ አምነዋል። የኢትዮጵያ ነገሥታት “ሥዩመ እግዚአብሔር” ተብለው መጠራታቸውና የቤተክርስቲያን ጠባቂ መኾናቸው አውሮፓውያን ለዘመናት ሲፈልጉት የነበረው “ካህኑ ዮሐንስ” እዚህ እንዳለ እንዲያረጋግጡ አድርጓቸዋል።
ኢትዮጵያ የነበራትን ያንን ታላቅ ካህናዊና ንጉሣዊ ማንነት ጥላ፣ የባዕዳንን የውድቀት ፍርፋሪ ለቃሚ ከኾነችበት ቀን ጀምሮ “ሕመሟ” ጸንቶባታል።
ትውልዴ ፍጹም የአባቶቹን የማይመስል ክርስትና፦ እንከፍ ምስኪንነት፣ ሽልጥልጥ አስመሳይነት፣ ወኔቢስ ጃንደርባነት እንድ መንፈሳዊነት እየተጋተ ይጠፋል። በተለይም ወንዱ ቤተሰብ መሥርቶ የሚመራበት ወንድነት መክሊቱ፣ አባወራነቱ ይኮነናል።
ዛሬ የምናየው የቤተሰብ መበተን፣ የትዳር መፍረስናና የሀገር መናወጥ በናቅነው፣ በጠላነውና በቀበርነው እሴት ማንነታችን ልክ የመጣ ነው።
ካህኑ ዮሐንስ የሚታወቀው በእምነቱ የጸና፣ ወኔው፣ ጀግንነቱ የማይበገር፣ በሥልጣኑ ባለግርማና በስብዕናው ፍጹም አባወራ ኾኖ ነው።
ይህን ማንነት ነው ዛሬ ላለው ትውልዴ የምነግረው፣ በተለይም ከወንዱ ዘንድ እንዲመለስ የምመኘው “ባለግርማና የጠንካራ ስብዕና” ባለቤት የኾነ አባወራ!



0 Comments